አዋጅ ቁጥር ፮ ፻ ፵ ፰/፪ሺ፩
የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግሥት የፋይናንስ አስተዳደርን ለመደንገግ የወጣ አዋጅ
የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግሥት የፋይናንስ አስተዳደር አዋጅ ሥራ ላይ በቆየባቸው ዓመታት ያጋጠሙ የአፈጻጸም
ችግሮችን በማስወገድ የመንግሥት በጀት አዘገጃጀት፣ የመንግሥት ገንዘብ አሰባሰብ፣ የክፍያ፣ የሂሳብ አያያዝ እና
የውስጥ ቁጥጥር እንዲሁም የሀብትና የዕዳ አስተዳደር ብቃት ያለው፣ ቀልጣፋ እና ውጤታማ እንዲሆን ለማድረግ
አዋጁን ማሻሻል አስፈላጊ መሆኑ ስለታመነበት፣
የመንግሥት የፋይናንስ አስተዳደር ሥርዓት ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ለማድረግ በሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ
ፕሮግራም የተካሔደው ጥናት ውጤት የሆኑትን አዳዲስ የአሠራር ሥርዓቶች ሥራ ላይ ማዋል አስፈላጊ ሆኖ
በመገኘቱ፣
በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ሕገ መንግሥት አንቀጽ ፶ ፭(፩) መሠረት የሚከተለው ታውጇል
ክፍል አንድ ጠ ቅ ላ ላ
፩. አጭር ርዕስ
ይህ አዋጅ ‹‹የኢትዮጵያ ፌዴራል መንግሥት የፋይናንስ አስተዳደር አዋጅ ቁጥር ፮ ፻ ፵ ፰/፪ሺ፩›› ተብሎ ሊጠቀስ
ይችላል
፪. ትርጓሜ
የቃሉ አገባብ ሌላ ትርጉም የሚያሰጠው ካልሆነ በስተቀር በዚህ አዋጅ ውስጥ-
፩/ ‹‹በዓይነት የተሰጠ እርዳታ›› ማለት የፌዴራል መንግሥት ከገንዘብ ሌላ በዕቃ ወይም በአገልግሎት መልክ በሁለት
ወይም በባለብዙ ወገን ስምምነት ወይም ከሌሎች ምንጮች የሚቀበለው ማናቸውም እርዳታ ነው፤
፪/ ‹‹ማፅደቅ›› ማለት ከተጠቃለለው ፈንድ ላይ ለመክፈል የሚያስችል በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሚሰጥ
ማናቸውም ሥልጣን ነው፤
፫/ ‹‹መፍቀድ›› ማለት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፀደቀው በጀት ሥራ ላይ እንዲውል ከሚኒስትሩ የሚገኝ
ይሁንታ ነው፤
፬/ ‹‹የካፒታል ወጪ›› ማለት ቋሚ ሀብት ለማፍራት ወይም ለማሻሻል ወጪ የሚደረግ ገንዘብ ሲሆን ለሥልጠና፣
ለምክር አገልግሎት እና ለምርምር የሚደረገውን ወጪ ይጨምራል፤
፭/ ‹‹የተጠቃለለ ፈንድ›› ማለት በዚህ አዋጅ መሠረት በማናቸውም የመንግሥት መሥሪያ ቤት ስም በሚኒስቴሩ
በተከፈተው የባንክ ሂሣብ ውስጥ ገቢ የተደረገ የመንግሥት ገንዘብ፣ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ለክፍያ እንዲውል
በጥሬ ገንዘብ የያዙት እንዲሁም በዓይነት የተገኘ እርዳታ ነው፤
፮/ ‹‹ግዴታ›› ማለት በውል፣ በስምምነት ወይም በሕግ የተመለከቱት ሁኔታዎች ሲሟሉ የሚፈጠር ኃላፊነት ነው፤
፯/ ‹‹ክፍያ›› ማለት በተጠቃለለው ፈንድ ውስጥ የተቀመጠውን የመንግሥት ገንዘብ ለተፈቀደለት የመንግሥት
መሥሪያ ቤት ወይም ሌላ አካል ማስተላለፍ ነው፤